ሩህ ሚዲያ – Ruh Media

Find articulated views on the Fabrics of Ethiopian society & the world at large. There is no limit of topics of address: culture, lifestyle, history, art, literature, politics and economy. Habtamu Girma's page shares opinions, viewpoints, and/or commentaries on issues that matters for us all!!!

ሩህ ሚዲያ የተለያዩ የዲጂታል የብዝሃ-መገናኛ አማራጮችን በመጠቀም በአፍሪካ፣ በተለይ በኢትዮጵያ የኢኮኖሚ አስተዳደርና ፖሊሲ፣ ፖለቲካል ኢኮኖሚ፣ ጂኦ-ኢኮኖሚክስ፣ ጂኦ-ፖለቲካ ጉዳዮች ዙሪያ በእውቀትና በዕውነት የተቀረጹ መረጃዎችን ለህዝብ ማድረስን ዓላማው ያደረገ ሚዲያ ነው፤ ዓላማውም በአገራዊ ኢኮኖሚያዊ አጀንዳዎች ላይ የሚኖረን ግንዛቤ በጥናትና በዕውቀት የተደገፈ እንዲሆን ጥረት ማድረግ ነው፤ በሩህ ሚዲያ ውስብስብ የሆኑ የኢኮኖሚ ጽንሰ ሃሳቦች እና የፖሊሲ እርምጃዎችን በቀላሉ ህዝብ በሚረዳው መንገድ ለማቅረብ ጥረት ይደረጋል // Ruh Media is aimed at addressing contextual factors associated to African economy, politics, geo-economics, natural resource conservation & management, climate change and energy transition issues. Ruh Media produces original contents capturing the human stories behind statistics, and showing how continental (African) and Ethiopian specific developmental aspirations translate into community-level change // የሩህ ሚዲያ ድህረ ገጽና የማህበራዊ ሚዲያ ገጾችን ይጎብኙ፤ ይወዳጁ!

አለማችን በኮሮና ወረርሽኝ መናጋትም፣ መረጋጋትም ገጥሟታል

ሀብታሙ ግርማ
መጋቢት 24 ቀን 2012 ዓ.ም
ጅግጅጋ፣ ኢትዮጵያ



አለም በጦር መሳሪያ እሽቅድምድም ሲባዝን ከርሞ፤ የህብረተሰብ ጤና ጉዳይ ተዘንግቶ፤ ይኸው የአለማችን ባለጸጋ ቢልጌትስ ከሶስት አመታት አስቀድሞ እንደተነበየው የጭንቅ ቀን መጥቷል። አሁን አገራት በገፍ ያከማቹትን የጦር መሣሪያ ኮሮና ቫይረስን ለመውጋት ሊጠቀሙበት አልቻሉም፤ አይችሉም። እንዲያው ለሰው ሰራሽ ጦርነት የተዘጋጁበትን ቁራሽ ያህል እንኳ ለህብረተሰብ ጤና ጉዳይ ቢመራመሩበት ኮሮና ዛሬ አይሰለጥንብንም ነበር።

ዛሬ አለም ለዚህ ዝንጉነቷ ዋጋ እየከፈለች ነው።

የአሜሪካ መንግስት ያለፉትን ሃያ አመታት ሲባዝንበት የቆየው የአልቃይዳ መራሹ የ9/11 የሽብርተኝነት ጥቃት የገደለው 2977 አሜሪካዊያንን ነበር። ነገር ግን የናቁት የወረረሽኝ ስጋት ህዝባቸውን እየፈጀ ነው። በአሜሪካን አገር ኮሮና በአንድ ሳምንት ብቻ 3177 ዜጎችን ለህልፈት ዳርጓል።

ይህ የሞት አሃዝ በትንሹ አንድ መቶ ሺህ ሊያሻቅብ እንደሚችል ፕሬዚዳንት ትራምፕ ከትናንት በስቲያ ለአሜሪካዊያን መርዶ አርድተዋቸዋል።

እንግዲህ የአለም የጦርነት ጋሬጣን በየክፍለ አለሙ የፈጠረች እና እየፈጠረች መሳሪያ በመሸጥ ኢኮኖሚዋን ስታሞቅ ከርማ አሁን ሂሳብ እያወራረደች ነው፥ አሜሪካ። የአለም አገራትም (ኢትዮጵያን ጨምሮ) እንዲሁ ነው።

አሜሪካ የአለም ፖሊስ ናት (ራሷን የሾመች) ሲባል ትርጉሙ ግልጽ ነው። የአሜሪካ ጦስ በሁሉም የአለም ጫፍ አለ ማለት ነው። ይህ ጦሷ ለእኛ ለኢትዮጵያዊያን በበርካታ ጊዜያት የህልውና አደጋን ደቅኖ ኖሯል፤ ከጎሮቤቶቻችን የአፍሪካ እና የአረብ አገራት ጋር በጥርጣሬ እየተያየን ለዘመናት ቆይተናል፤ ባለፉት ሁለት አመታት በጠቅይ ሚኒስትራችን የግል ጥረት ከኤርትራ እና ግብጽን ጨምሮ፣ከበርካታ የአረብ መንግስታት ጋር ወዳጅነት መስርተን ሰላምን ማጣጣም እንደጀመርን አሜሪካ በናይል ወንዝ ውዝግብ የአደራዳሪ ካባ በመልበስ ይኸው የኢትዮጵያን እና የአረብ አገራትን ወደ ዳግም ቁርሾ ካስገባች አንድ ወር እንኳ አልሞላትም።
በዚህ አጭር ጊዜ ውስጥ ግን ኮሮና ቫይረስ ገብቶ የማረጋጋት ሥራ ሰርቷል ማለት ይቻላል።

በኢትዮጵያ ላይ ጦር ለማዝመት ላይ ታች ሲሉ የከረሙት የግብጽ የወታደራዊ ፊት አውራሪዎች ባለፉት ሁለት ሳምንታት የኮሮና ወረርሽኝ ገፈት ቀማሾች ሆነዋል፤ ኢትዮጵያ ላይ ያደሙት እና ግልጽ የጦርነት አዋጅ ያስነገሩት የአረብ ሊግ አባል አገራት አሁን በኮሮና ተወጥረው እያቃተቱ ናቸው።

በትራምፕ መሪነት አሜሪካ የአለም የትብብር እና የአብሮነት እሴቶችን አጥፍታ አክራሪ ብሔርተኝነት በመላው አለም ሰፍኖ፤ ሶስተኛው የአለም ጦርነት ፊሽካ መነፋት በስጋት እየጠበቅን ሳለን ግን ኮሮና በድንገት ከተፍ ብሎ የማረጋጋት ስራ እየሰራ ነው።

ቀድሞ የጠላት ያህል ይተያዩ የነበሩ፣ እንደ እስራኤል እና ፍልስጤም ያሉ አገራት እንኳ በኮሮና ወረርሽኝ ምክንያት ሊተባበሩ ግድ ብሏቸዋል።

ወደ ኢትዮጵያ ስንመጣም፣ ኮሮና በአገሪቱ ሊከሰት ቋፍ ላይ የነበረውን ብሄር ተኮር የህዝብ ለህዝብ (ሲቪል) ጦርነት እና እልቂት አደጋ ረገብ አድርጎታል። ኮሮና ብሔር ለይቶ አያጠቃም፤ እንሰሳትን እንኳ አያጠቃም።የሚያጠቃው ሰውን ብቻ ነው። በሽታው ከሰው ወደ ሰው በፍጥነት የሚዛመት ስለሆነ ለአንዱ ሰው መዳን ዋስትና የሌላው ሰው ጤነኛ መሆን ነው፤ ስለሆነም አብሮ ለመክረም ካስፈለገ አንድ ሰው ለራሱ ሲል የሌሎች ሰዎችን ጤንነት (ደህንነት) ግድ እንዲሰጠው በሽታው አስገድዶታል።

በመሆኑም ቢያንስ ኮሮና ቫይረስ በአገሪቱ እስካለ ድረስ በኢትዮጵያ ሰው የሚፈላለገው በብሔሩ ሳይሆን በሰውነት መስፈርት ብቻ ነው። እናም የኮሮና ወረርሽኝ መተባበር፣ መተሳሰብ እና አንድነትን በግድም ቢሆን አምጥቷል።

የእኛ ጥንቃቄ ፣ እንዲሁም የፈጣሪ ቸርነት ታክሎበት ከመጣብን መቅሰፍት እንደምንወጣ እምነት አለኝ። ታዲያ በጭንቅ ወቅት ያገኘነው የአንድነት መንፈስ በሰላሙም ጊዜ ይቀጥል ይሆን? ለሁሉም ጊዜ መልስ አለው!


Discover more from ሩህ ሚዲያ – Ruh Media

Subscribe to get the latest posts sent to your email.

Posted in

አስተያየት ያስቀምጡ

ይህ ጣቢያ አይፈለጌ መልዕክትን ለመቀነስ Akismet ይጠቀማል። የአስተያየትዎ ውሂብ እንዴት እንደሚሰናዳ ይወቁ

Discover more from ሩህ ሚዲያ - Ruh Media

Subscribe now to keep reading and get access to the full archive.

Continue reading